Wednesday, November 4, 2009

ውድ የቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን አባላት ሆይ!!
አበው ሲተርቱ “ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል” እንዲሉ፤ እነ የቦርድ አባላት
የሚዘርፉት ሳያንስ በየአገልግሎት ኮሚቴው የተመረጡት ሁሉ የሹመት ምልክት መበዝበዝ ነው፤
ካልሆነም እንደስልጣን መጠቀም ነው፤ እያሉ በቦርዱና በየኮሚቴዎቹ ተሰግስገው
ቤተክርስቲያናችንን ሲያራቁቱ ምእመናኑን ሲያደሙ መቆየታቸው ከኛ አልፎ በአለም ዙሪያ ባሉ
አብያተክርስቲያናት እና ኢትዮጵያውያን ሲነገር መስማቱ የሚያሳፍርና የሚያሳዝን ነው። ጌታችንና
መድሀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቤተመቅደስ ሲሸጡና ሲለውጡ እንዲሁም ብዙ ጸያፍ
አድራጎትን ሲፈጽሙ ስላገኛቸው ሃሳውያን ሲናገር “ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል፤ እናንተ ግን
የሌቦች ዋሻ፤ የቀማኞች መሸሻ አደረጋችሁት” ብሏል (የማቴዎስ ወንጌል ፳፩፡፲፪)። እኛም እዚሁ
ቁጭ ብለን እኒሁ በዝባዦች “ቤተክርስቲያኗን የመሰረትናት እኛ ነን፤ ሌላው ሰው ምን አባቱ
አገባው፤ እንኳን መዝረፍ ምንስ ብናደርግ” በማለት ሲመጻደቁ እየሰማን፤ የሚያደርጉትን
አያውቁምና ይቅር በላቸው! ስንል ቆይተናል። በጥቂቱ ለመጥቀስ፦ የስለት፤ የሙዳየ
ምጽዋት፤የበጎ አድራት፤ የእደሳ፤ የጥገና፤ የእቃ ግዥን ጨምሮ ሲዘረፍ የኖረውን መጥቀስ
ይበቃል። አሁን ግን የተሾሙት የሚወርዱበት የዘረፉት ወደሕግ ፊት የሚቀርቡበት ቀን
እየተቃረበ ስለመጣ፤ የዚህ አይነት ጸያፍ ባህል ተካፋይ አንሆንም በማለትና በተለያየ ምክንያት
ከቤተክርስቲያን የራቃችሁ ሁሉ እንድትመለሱና እግዚአብሔርን በምትችሉት መንገድ ሁሉ
እንድታገለግሉ ከፍተኛ ጥሪ እናቀርብላችኋለን። የፈለጉትን ያድርጉ እኔ ምን አጨቃጨቀኝ
የሚባልበት ዘመን አልፎ፤ የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር የቄሳርን ለቄሳር ስጡ የሚለውን
መመሪያ በተግባር የምናውልበት ዘመን መጥቷል።
የአስተናጋጅ ኮሚቴ ዋና ሆነው የተመረጡትም በነአለማየሁ አስተዳዳሪነት ወቅት በማህበረ
ቅዱሳን ሙዳየ ምጽዋት ሰብሳቢነት ጊዜ ይችን ለናንተ ይችን ለኛ እየተባባሉ ሲበዘብዙ
መኖራቸው ለናንተ ለምታውቋቸው ስውር ነገር አይደለም።
በጣም የሚያስገርመው ደግሞ ያ ሁሉ ካለፈ በኋላ አሁንም ወደበፊቱ አሰራር
እንድንመለስ ባለቤታቸውን እና ግብርአበራቸውን በቤተክርስቲያን ውስጥ በሃሰት ለመመስከር
ይሉኝታ የሌለውን ጸሃፊ በድጋሜ ለማስመረጥ እየተሯሯጡና በየቦታው ጓደኞቻቸውን እየተማጠኑ
መሆናቸውን ሰምተናል።
አልፎ ተርፎም ምክትላቸውን አስመራጭ ኮሚቴ አስገብተዉ ይሄ የማይገኝ ስልጣን
ስለሆነ ተጠቀምበት ብለዉ ስላዘዙት እሱም በበኩሉ በየቀሳውስቱ ሳይቀር እባክዎ አማልዱኝ፤ ዋና
ጸሃፊዉና የአለቃየ ባለቤት እንድትመረጥ እርዱኝ እያለ መማጠኑን ደርሰንበታል። ይህ ግለሰብ
አስመራጭ ኮሚቴ መግባቱ ህዝብን በቅን መንፈስ እንዲያገለግል እንጅ ለመጠቀሚያ
አለመመረጡን ያስተማረው ስለሌለ አስመራጭ ኮሚቴ ገብቶ እከሌንና እከሌን ብቻ ምረጡ እያለ
ሊበጠብጥ ነው ማለት ነው።
ካሁን ቀደም እንደገለጽነው ለአስተዳደር ቦርድ አንድ ግለሰብ ሲመረጥ ኑሮውንና ጉልበቱን ለኔ
ሳይል በበጎ ፈቃድ ለእግዚአብሄር እንዲሰጥ ሲጠየቅ ብዙወች ቶሎ እሽ ስለማይሉ እየተለመኑና
እየተማጠኑ ነበር የሚመረጡት።
እዚህ ቤተክርስቲያን ግን ለቦርድ አገልግሎት መመረጥ እንደ አገራችን ሹመት ስለሚመስላቸው
ከምረጡኝና አስመርጡኝ አልፎ እከሌና እከሌን መምረጥ አለባችሁ የሚባል በሽታ መጥቷል።
ከተመረጡ በኋላም ጊዜአቸውን ሲጨርሱ አንወርድም የሚሉም አልታጡም። ይሉኝታም
ኃፍረትም ቀርቷል፤ ዘረፋው በይፋ ቀጥሏል። የሌባ አይነደረቅ መልሶ ልብ ያደርቅ እንደሚባለው
ያለደረሰኝ የሚሰበሰበው ገንዘብ የት እይገባ እንደሆነና አላማውም ምን እንደሆነ በሚቀጥለው
እትም እንገልጻልችኋለን። በቸር ይግጠመን!!

No comments:

Post a Comment